ሱዳናውያን ወታደራዊ መንግስታቸውን መቃወማቸውን ቀጥለዋል
ሱዳናውያን ወታደራዊ መንግስታቸውን በመቃዎም አሁንም ሰላማዊ ሰልፍ ማድረጋቸውን ቀጥለዋል፡፡
ባለፈው አመት የተካሄደውን መፈንቅለ መንግስት በመቃወም በሺዎች የሚቆጠሩ ሱዳናውያን በካርቱም ፕሬዚዳንታዊ ቤተ መንግስት ፊት ለፊት ባደረጉት ሰልፍ አንድ ሱዳናዊ ተቃዋሚ በጥይት ተመትቶ መሞቱን የህክምና ባለሙያዎች ተናግረዋል።
ጄኔራል አብዱልፈታህ አል-ቡርሃን ባለፈው አመት ጥቅምት 25 ወታደራዊ መፈንቅለ መንግስት ካደረጉ በኋላ በተደረጉ የተቃውሞ ሰለማዊ ሰልፎች የሞቱ ሰዎች ቁጥር 84 መድረሱን ገለልተኛ የህክምና ባለሙያዎች ቡድን አስታውቋል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰባዊ መብት ባለሙያ የሆኑት አዳማ ዲንግ ወደ ሱዳን በሄዱበት ወቅት የሱዳን ባለሥልጣናት በተቃዋሚዎች ላይ የሚወስዷቸው እርምጃዎች እንዳሳሰባቸው ገልፀዋል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅትም በተመሳሳይ የሱዳን ተቃዋሚዎች ጉዳይ እንደሚያሳስበው የገለፀ ሲሆን ሁከቱ በዚህ የሚቀጥል ከሆነ ተጨማሪ መዘዞች ሊመጡ እንደሚችሉ ያለውን ስጋት ገልጿል፡፡
የሱዳን የቅርብ ጊዜ መፈንቅለ መንግሥቱ ሰፊ ዓለም አቀፍ ውግዘት እያጋጠመው ሲሆን ሀገሪቱ ያላት ዲፕሎማሲየዊ ግንኙነት እንዲቀዛቀዝ ምክንያት መሆኑን አፍሪካ ኒውስ በዘገባው አስታውቋል፡፡ (ኤፍ ቢሲ)